2021-01-15 17:25:50
ለቸኮለ! ዐርብ ጥር 7/2013 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች
1፤ በትግራይ ክልል ገጠራማ አካባቢዎች በቀጠለው ግጭት ስለ ሰላማዊ ሰዎች ጉዳት እና ግድያ የሚወጡ ሪፖርቶች እጅጉን አሳሳቢ እንደሆኑ የተመድ ሰብዓዊ ዕርዳታ ማስተባበሪያ ቢሮ ቃል አቀባይ ጄንስ ላርክ ዛሬ ከጄኔቫ መናገራቸውን ከድርጅቱ ፌስቡክ ገጽ ተመልክተናል። በክልሉ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዕርዳታ ፈላጊዎች ገና ዕርዳታ አለማግኘታቸው አሳሳቢ እንደሆነም ገልጠዋል። ለሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦቱ ማነቆ የሆኑትን የጸጥታ ችግር እና የፌደራል እና ክልል መንግሥታት ቢሮክራሲያዊ ማነቆዎችን ሁሉም ወገኖች በአፋጣኝ እንዲፈቱም ቃል አቀባዩ ተማጽነዋል።
2፤ በአዲስ አበባ ከተማ የተገነባው አዲሱ ሸገር ዳቦ ፋብሪካ ባለፉት 5 ወራት 70 ሚሊዮን ብር ከስሬያለሁ ማለቱን ኢትዮ ኤፍኤም ዘግቧል። ለኪሳራ የተዳረገው የምርት ግብዓቶች ወጭ ከፍተኛ በመሆኑ እንደሆነ የጠቀሰው ፋብሪካው፣ ከመዘጋት ለማዳን መንግሥት ስንዴ እና ሌሎች ግብዓቶችን እንዲያቀርብለት ጠይቋል። ቀደም ሲል ከአዲስ አበባ አስተዳደር ድጋፍ ጠይቆ ምላሽ እንዳላገኘም ገልጧል። ፋብሪካው በቀን ከ700 እስከ 800 ሺህ ዳቦ እያመረተ ሲሆን፣ የዳቦ ማከፋፈያ መኪና ዕጥረት ግን ትልቅ ችግር ሆኖብኛል ብሏል።
3፤ የደቡብ ክልል ምክር ቤት ዛሬ በጀመረው አስቸኳይ ጉባዔ በየእርከኑ ላሉ ምክር ቤቶች በቀጣዩ ክልላዊ ምርጫ የሚኖራቸውን የተወካይ ብዛት የሚወስን አዋጅ አጽድቋል። ለክልል ምክር ቤት ምርጫ፣ ከ7 ወረዳዎች በታች ባላቸው ዞኖች 10 ተወካዮች፣ ከ7 ወረዳዎች በላይ ላሏቸው 5 ተወካዮች እንዲመረጡ አዋጁ ደንግጓል። ለወረዳ ምክር ቤቶች እና ለከተማ አስተዳደሮች ደሞ ከየቀበሌው 5 ተወካዮች ይመረጣሉ። ለዘንድሮው ክልላዊ ምርጫ አዳዲስ የምርጫ ክልሎች እንደማይኖሩ የክልሉ መንግሥት አስታውቋል።
4፤ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ለምርጫ ክልሎች የመለመላቸውን የመጀመሪያ ዙር ዕጩ የምርጫ አስፈጻሚዎች ለፖለቲካ ፓርቲዎች ለማሳወቅ ዝግጁ እንደሆነ በማኅበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል። ሕጋዊ ምዝገባ ያጠናቀቁ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለምርጫ ክልሎች የተመለመሉ የምርጫ አስፈጻሚዎችን ዝርዝር ከቦርዱ ጽሕፈት ቤት እንዲወስዱ እና በገለልተኛነታቸው ላይ አስተያየት እንዲሰጡበትም ጥሪ አድርጓል። በቀጣይ ጊዜያትም ቀሪዎቹን የምርጫ አስፈጳሚዎች ለፓርቲዎች ይፋ አደርጋለሁ- ብሏል ቦርዱ። በመጀመሪያው ዙር ስንት የምርጫ አስፈጻሚዎችን እንዳዘጋጀ ግን ቦርዱ አልገለጸም።
5፤ ጎረቤት ደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያን እና ሱዳንን ድንበር ውዝግብ ለማደራደር ዝግጁነቷን መግለጧን የሱዳን ሉዓላዊ ሽግግር ምክር ቤት ዛሬ ማስታወቁን ዥንዋ ዘግቧል። የሉዓላዊ ምክር ቤቱ ሊቀመንበር ጀኔራል አብዱል ፈታህ አል-ቡሕራን ይህን ዛሬ ያስታወቁት፣ ከደቡብ ሱዳኑ ፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር ጸጥታ አማካሪ ቱት ጋትሉክ ጋር በጉዳዩ ላይ ከተነጋገሩ በኋላ ነው። ደቡብ ሱዳን በዐለማቀፍ ደረጃ በታወቁ ድንበሮች አማካኝነት ለማደራደር እንደምትፈልግ ጋትሉክ ተናግረዋል ተብሏል።
6፤ ሱዳን ከኢትዮጵያ ጋር የሚያዋስናትን ምሥራቃዊ ድንበር በኩል ያለውን የአየር ክልሏን ከትናንት ጀምሮ እንደዘጋች ሱዳን ትሪቡን ዘግቧል። ሱዳን በገዳሪፍ ግዛት በኩል የአየር ክልሏን የዘጋችው፣ የኢትዮጵያ ተዋጊ አውሮፕላን የአየር ክልሌን ጥሶ ገብቷል የሚል ውንጀላ ባሰማች ማግስት ነው።
7፤ ወደ ኢትዮጵያ ለሥራ የሚጓዙ ግብጻውያን በቅድሚያ ካይሮ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ የመግቢያ ቪዛ ማግኘት እንዳለባቸው በአዲስ አበባ የግብጽ ኢምባሲ ማሳሰቡን አሕራም ጋዜጣ ዘግቧል። ከአፍሪካ ኅብረት ጋር ሥራ ያላቸውም፣ ለመግቢያቸው በቅድሚያ ኅብረቱ ከኢትዮጵያ መንግሥት ፍቃድ ማግኘቱን እንዲያረጋግጡ ኢምባሲው መክሯል። እስካሁን ባለው አሠራር ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ግብጻውያን ቪዛ የሚያገኙት ቦሌ ዐለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ነበር። [ዋዜማ ራዲዮ]
13.1K views14:25